የአማራ ክልል ምክር ቤት ሴቶች ሕጻናት ማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የሚከታተሏቸውን የትምህርት ቢሮ፣ የጤና ቢሮ፣ የሴቶች ሕፃናት ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ እና የሲቪልና ቤተሰብ አገልግሎት የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ገምግሟል።
የተቋማቱ የሥራ ኀላፊዎች የተቋማቸውን አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበዋል። ቋሚ ኮሚቴውም የቀረበውን ሪፖርት በመከታተል አስተያየት እና ጥያቄዎችን ያነሳ ሲኾን ሪፖርቱን ያቀረቡ የተቋማቱ የሥራ ኀላፊዎች ምላሽ ሰጥተውባቸዋል።
በክልሉ ምክር ቤት የሴቶች ሕፃናት እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሠብሣቢ አበራሽ ታደሰ በጀት ዓመቱ ኹሉም ተቋማት ያቀዷቸውን ተግባራት ከመፈጸም፤ ከበጀት አጠቃቀም፤ ከኦዲት ግኝት ፤ ከተሻጋሪ ሥራዎች እና ከሌሎች ተግባራት አኳያ ውጤታማ ሥራ ያከናወኑበት ዓመት መኾኑን ተናግረዋል።
ቋሚ ኮሚቴው በተቋማቱ አፈጻጸም በጥንካሬ የተከናወኑ እና ተጠናክረው መቀጠል ያለባቸውን እንዲኹም በቀጣይ ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገቡ ጉዳዮችን አንስቷል።
የተማሪዎች ምዝገባ ላይ ከዕቅድ አኳያ ብዙ የሚቀር ቢኾንም ከባለፈው ዓመት አኳያ የተሻለ የተማሪዎች ምዝገባ መከናወኑ፤ አዳሪ፣ ሞዴል እና የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶችን ግንባታ ለማስጨረስ እንዲኹም ለፈጠራ እና ለምርምር የተሰጠው ትኩረት የሚበረታታ መኾኑም ተነስቷል።
የኢኮኖሚ አቅማቸው ዝቅተኛ ለኾኑ ተማሪዎች የተከናወነው የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ፤ የምገባ አገልግሎት እና መሰል በጎ ተግባራት ውጤታማ ቢኾኑም በዕቅዱ ልክ ለመፈጸም ጥረት መደረግ እንዳለበትም ተመላክቷል። የቁሳቁስ ድጋፍ ፍትሐዊነት እና የምገባ ዕቅድን ከመፈጸም አኳያ ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል ተብሏል።
ጤና ቢሮው የኢኒሸቲቭ ተግባራትን በመፈጸም፤ ባለሙያን በማብቃት፤ ይነሱ የነበሩ የመልካም አሥተዳደር ችግሮችን በመፍታት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው ተብሏል። ጤና ቢሮን መልሶ በመገንባት ምቹ የሥራ ከባቢን ከመፍጠር እና የጤና ተቋማትን ከመገንባት አኳያም አመርቂ ሥራ መከናወኑ ተገልጿል።
የሕክምና መሣሪያዎችን የማሟላት፤ የማኅበረሰብ መድኃኒት ቤቶች በመገንባት ማኅበረሰቡ በቅርበት የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኝ የተከናወነው ሥራም የሚበረታታ መኾኑ ተነስቷል።
ቋሚ ኮሚቴው በቀጣይ በተቋማቱ ትኩረት እንዲሰጣቸው ካስቀመጣቸው ጉዳዮች መካከልም፦
ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የተማሪዎች ተሳትፎ፤ ለአካል ጉዳተኞች ክፍያ እና ምቹ ሁኔታ መፍጠር፤ ለጎልማሶች ተግባር ተኮር ትምህርት፤ ከደረጃ በታች የኾኑ ትምህርት ቤቶችን ደረጃ ማሻሻል ላይ በትኩረት መሥራት ይገባል ተብሏል።
የሕጻናት እና አካል ጉዳተኞች የአዕምሮ ዕድገት እና የግብረ ገብ ትምህርት ላይ በቂ ሥራ ስላልተሠራ ቀጣይ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ተመላክቷል።
በጥቅሉ በ2018 ዓ.ም ተቋማት በዕቅዳቸው ልክ ለመፈጸም ያደረጉት ርብርብ እና የተገኘው ውጤት ካለፉት ዓመታት አኳያ የተሻሉ ውጤቶች የተመዘገቡበት መኾኑ ተነስቷል።



